የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የልደት በዓል ተከበረ

&nbsp

ክርስቶስ ተንስአ እሙታን…….በዐቢይ ኃይል ወስልጣን

አሰሮ ለሰይጣን ………….አግአዞ ለአዳም

ሰላም…………እምይእዜሰ

ኮነ …………….ፍስሀ ወሰላም

&nbsp

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የልደት በዓል ተከበረ።

“እም ሐና ወኢያቄም ተወለድኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ – በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ” – አባ ሕርያቆስ

ሰማይና ምድርን የፈጠረ፣ ፈጥሮም የሚመግብ ንጉሠ ሰማይ ወምድር የሆነን የእግዚአብሔር ቃል ለመቀበል የተገባት ሆና የተገኘች፣ አምላክን የወለደች የባህርያችን(ሰውነት) መመኪያ የሆነች የእመቤታችን ቅድስተ ቅዱሳን ንጽኅተ ንጹኃን ድንግል ማርያም የልደት በዓል ግንቦት ፩፣ ፳፻፰ዓ.ም. (ሜይ 09፥2016) በአጥቢያችን በደማቅ ሁኔታ ተከበረ። መርሐ ግብሩ በጸሎት ከተጀመረ በኋላ በተዓምረ ማርያም “ሰላም ለኪ ኦ ሐና እማ ለጸሐየ ጽድቅ ወላዲቱ ወምሕየውቱ ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ – ጸሐየ ጽድቅ የተባለ ክርስቶስ የምትወልድ እናት እና የጽድቁ ጸሐይ አያት የምትሆኝ ሐና ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ” ተብሎ እንደተመዘገበ የተስፋችን ሁሉ መፈፀሚያ የሆነች እመቤታችንን እና ወላጆቿን ክብር የሚያወሳ ሰፋ ያለ ትምህርት በመጋቤ ሐዲስ መምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማንአየ ተሰጥቷል፤ እመቤታችንን የሚያወድሱ ያሬዳዊ ዝማሬዎችም ተዘምረዋል።

ከመርሐ ግብሩ ፍጻሜ በኋላ ከሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ደጅ ላይ በመሰባሰብ የተዘጋጀው ጸበል ጸዲቅ ከተቀመሰ በኋላ ዝማሬዎች በማኅበር ተዘምረው ምዕመናን ወደየቤታቸው በሰላም ተሸኝተዋል።

“በእንተ ሔዋን ተዐፅወ ኆኅተ ገነት፤ ወበእንተ ማርያም ድንግል ተርኅወ ለነ ዳግመ። ስለሔዋን የገነት ደጅ ተዘጋ፤ ዳግመኛም ስለ ድንግል ማርያም ተከፈተልን።” – ቅዱስ ኤፍሬም

ድንግል ሆይ የልደትሽ ቀን በእውነትም የልደታችን ቀን ነው!

የበዓሉን አከባበር በፎቶ ይመልከቱ!

የጌታችን ስቅለት እና ትንሣኤ በዓላት በልዩ ልዩ ሃይማኖታዊ ሥርዓቶች በደማቅ ሁኔታ ተከበረ

&nbsp

ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን

ሞተ ወኬዶ ለሞት

ለእለ ውስተ መቃብር

ወሀበ ሕይወተ ዘለዓለመ ዕረፍተ።

&nbsp

&nbsp

የ፳፻፰ ዓ.ም የጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት እና ትንሣኤ በዓላት በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሔም በድምቀት ተከበረ። በዓላቱ በአባታችን አባ ገብረ ማርያም ቢምረው እና መጋቤ ሐዲስ ምሥጢረሥላሴ ማንአየ መሪነት እና በርካታ ቁጥር ባለው ምእመን ሱታፌ በተለያዩ አገልግሎቶች ተከብረዋል።

ዕለተ አርብ ሚያዝያ ፳፩፥፳፻፰ ዓ.ም በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መሠረት የጌታችንን ስቅለት በሚያወሱ ምንባባት፣ ሕማሙን በሚዘክሩ ጸሎቶች እንዲሁም በስግደት ያለፈ ሲሆን፤ “አምላክ ዓለምን ከፈጠረበት ይልቅ ሰው ሆኖ ዓለሙን ያዳነበት ጥበብ ይበልጣል” እንደተባለ የጌታችንን ረቂቅ የማዳን ሥራ እና ነገረ-መስቀሉን በተመለከተ በመጋቤ ሐዲስ ምሥጢረሥላሴ ትምህርት ተሰጥቷል።

ቅዳሜ ማለዳ ለቀዳም ስዑር እለት የሚደረጉት ጸሎትና ምንባባት ከተከናወኑ በኋላ ቀኑን የተመለከተ አጠር ያለ ትምህርት በመጋቤ ሐዲስ ምሥጢረሥላሴ ተሰጥቶ የማለዳው መርሐ ግብር ፍጻሜ ሆኗል።

ቅዳሜ ምሽት ከ 22:00 ሰዓት ጀምሮ የጌታችንን ትንሳዔ የሚያወድስ ሥርዓት ከምንባባትና ወረቦች ጋር ከተከናወነ በኋላ በኪዳንና በሥርዓተ ቅዳሴ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል። በዓሉን ለመካፈል የተገኘውም ህዝበ ክርስቲያንም ለበዓሉ የተዘጋጀውን የጾም መፈሰኪያ ጸበል ጸዲቅ እየቀመሰ ወደየቤቱ በሰላም ተመልሷል።

የበዓሉን አከባበር በፎቶ ይመልከቱ!

በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ በትሮንዳሔም የሆሳዕና በዓል በድምቀት ተከበረ።

በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሔም ሚያዝያ ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የሆሳዕና በዓል በጸሎት፣ በስብከተ ወንጌል እና በያሬዳዊ ዝማሬዎች እጅግ በርካታ የትሮንዳሔምና የአካባቢው ምዕመናን በተገኙበት በድምቀት ተከበረ።

በዕለቱ “እምአፈ ደቂቅ ወሕፃናት አስተዳሎከ ስብሐተ/ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ” (መዝ. ፰፥፪) ተብሎ እንደተጻፈ የቤተ ክርስቲያን የነገ ተስፋ የሆኑት ሕፃናት እና ታዳጊዎች በጣፈጠ አንደበታቸው በዓሉን የሚያወሱ ዝማሬዎችን አቅርበዋል። በመቀጠልም እለቱን የተመለከተ ትምህርት ከተሰጠ በኋላ መርሐ ግብሩ በጸሎት ተደምድሟል።

በመጨረሻም መርሐ ግብሩን የተሳተፈው ማኅበረ ምእመን ለበዓሉ የተዘጋጀውን ጸበል ጸዲቅ ለበረከት እየቀመሰ በሰላም ወደ ቤቱ ተሸኝቷል።

የበዓሉን አከባበር በፎቶ ይመልከቱ!

በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሔም የደብረ ዘይት በዓል በድምቀት ተከበረ

በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሔም መጋቢት ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓም የደብረ ዘይት በዓልን በቅዳሴ፣ በስብከተ ወንጌል እና በያሬዳዊ ዝማሬ ከስቶክሆልም ስዊድን የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ብርሃን አባ ገብረ ጊዮርጊስ ካሣዬን በመጋበዝ፤ በትሮንዳሄምና አካባቢው የሚገኙ ኦርቶዶክሳዊያን ምዕመናን በተገኙበት በዓሉ በድምቀት ተከብሯል።

በዓሉ በመካከለኛው አውሮፓ የስዓት አቆጣጠር ከንጋቱ 06:00 ሰዓት በጸሎት ተጀምሮ በዓሉን የሚያወሱ ከቅዱሳት መጽሃፍት በመነበብ የኪዳንና የቅዳሴ መርሃ ግብር ተካሂዷል። ከሥርዓተ ቅዳሴው በኋላ እለቱን የተመለከቱ የንስሃ መዝሙራት በአጥቢያው መዘምራን ቀርቧል። በመቀጠልም የደብረ ዘይት በዓልን በተመለከተ ሰፋ ያለ ትምህርት በመልአከ ብርሃን አባ ገብረ ጊዮርጊስ ቀረቦ የእለቱ መርሐ ግብር በአባታችን የማሳረጊያ ጸሎት ተፈጽሟል።

በመጨረሻም በመርሃ ግብሩ የተሳተፈው ምእመናን ወ ምእመናት ለበዓሉ የተዘጋጀውን ጸበል ጸዲቅ ለበረከት እየቀመሰ በሰላም ወደ ቤቱ ተሸኝቷል።

የበዓሉን አከባበር በፎቶ ይመልከቱ!

የሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ ዓመታዊ የንግስ ክብረ በዓል

TSGC-KibreBealMastawekia 7በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
 
የሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ ዓመታዊ የንግስ ክብረ በዓል ግንቦት ፭ እና ፮ በትሮንዳሔም ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ይከበራል።
የ፳፻፰ ዓ.ም. የሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ ዓመታዊ የንግስ ክብረ በዓል ከጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ትንሣኤ ጋር በመግጠሙ ከአባቶች ጋር በመነጋገር በተወሰነው መሰረት ክብረ በዓሉ ዓርብ ግንቦት ፭ እና ቅዳሜ ግንቦት ፮ ፣ ፳፻፰ ዓ.ም. ለማክበር ታቅዷል። 
በበዓሉ ላይ በርካታ የቤተክርስቲያን አባቶች ከተለያዩ የአውሮጳ ሀገራት እና ከሀገረ ኖርዌይ እንዲሁም መጋቤ ሐዲስ ምስጢረ ሥላሴ ማናዬ ከኢትዮጵያ እንደሚገኙ ይጠበቃል። ከዚህ በተጨማሪም ከመላው ኖርዌይ በሚሰባሰቡ ምዕመናን፣ የትሮንዳሔም ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን አባላት እና የቅዱስ ሚካኤል የኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አባቶች/ወንድሞች/እህቶች በተገኙበት በአንድነት በዓሉ በትሮንዳሔም በደማቅ ሁኔታ ይከበራል።
ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን፤ አሜን።

የ፳፻፰ ዓ.ም የልደት በዓል በድምቀት ተከበረ

የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሔም አጥቢያ በሚገኙ ምእመናን በደመቀ ሥርዓት በቅዳሴ፣ በዝማሬና በስብከተ ወንጌል አገልግሎት ተከብሮ ዋለ።

እሁድ ጥር ፩፥፳፻፰ በተጋበዙ አባቶችና ዲያቆናት በኪዳንና ቅዳሴ የተጀመረው መርሐ ግብር በአጥቢያው መዘምራን በዓሉን የሚያወድሱ ያሬዳዊ ዝማሬዎች በማቅረብ የቀጠለ ሲሆን በመጨረሻም የዕለቱ ስብከተ ወንጌል በአባቶች ተሰጥቶ ቅዳሴው ተፈጽሟል። ምእመናንም ለበዓሉ የተዘጋጀውን ዝክር ቀምሰው ወደየመጡበት በሰላም ተሸኝተዋል።

የበዓሉን አከባበር በፎቶ ይመልከቱ!

ቤተ ክርስቲያናችን መንበረ ፕትርክናው ኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ ስር በአስተዳደራዊ መዋቅር መታቀፏን ስለማሳዎቅ

letter1 107x151ቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅድመ ታሪኩ እ.ኤ.አ በ1995 መጨረሻ ላይ ለትምህርት ወደ ትሮንዳሄም፣ ኖርዌይ በመጡ ቀናኢ የቤተክርስቲያን ልጆች አማካኝነት በሰንበት ትምህርት ቤትነት ደረጃ በመቋቋም ነበር። ሰንበት ት/ቤት በነበረበት ወቅት እ.ኤ.አ በ2010 ህጋዊ ሆኖ በኖርዌይ ሀገር በሃይማኖት ተቋምነት የተመዘገበ ሲሆን ቅዱስ ጊዮርጊስ በመባል እ.ኤ.አ በ2012 በአቅራቢያው እየመጡ በሚያገለግሉን አባቶች ተሰይሟል። እ.ኤ.አ በ2013 ደግሞ ታቦተ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኢትዮጵያ በአባቶች ተባርኮ መጥቶ ከሰንበት ትምህርት ቤትነት ወደ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያንነት በማደግ ቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተመስርቷል። በዚህ ጉዞዋ ቤተ ክስቲያናችን በዚህ መዋቅር ነኝ ብላ ባታውጅም፤ ከአባቶቻችን እንደተማርነው ያለመዋቅርና ያለስርዓት መጓዝ ጥሩና አግባብ ባለመሆኑ /መዝ. ፻፲፰፥፻፲፰ ፡ ፩ኛ ተሰ. ፭፥፲፬ ፡ ፪ኛ ተሰ. ፫፥፮/ አጥቢያችን በአስተዳደራዊ መዋቅር ስር ገብታ ትተዳደር ዘንድ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያናዊና ሀይማኖታዊ ህግ መሆኑ ግልጽ ነው። ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው ይህን ሃይማኖታዊ ስርዓት ሰፊ ጊዜ በመውሰድ የተወያየበት ሲሆን ከአባቶችም ጋር እንደዚሁ በተለያዩ ጊዜያት ውይይት አድርጓል። ከዚህም በተጨማሪ ምዕመናን በጉዳዩ ዙርያ ሰፊ ግንዛቤ እንዲኖራቸውና ይህን አጀንዳ በሃይማኖትና በእምነት መነጸር ብቻ እንዲመለከቱት የሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት እና ቅዱስ ሲኖዶስ ለቤተ ክርስቲያን መተዳደርያ ህግ ይሆን ዘንድ ባወጣው ቃለ ዓዋዲ ላይ ሰፊ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ጥረት ተደርጓል።

 

ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ህግ አንፃር፣ እንዲሁም ይህች ቤተ ክርስቲያናችን ስትመሰረት ታቦተ ህጋችን በብፁዓን አባቶች ተባርኮ ከሀገር ቤት እንደመምጣቱ መጠን፤ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው ነገሮችን በእርጋታ ተመልክቶ የትሮንዳሔም ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን ቅዱስ ሲኖዶስ ስር እንድትሆን አቅጣጫ አስቀምጦ ለተግባራውነቱ በእግዚአብሔር መልካም ፍቃድ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል። በዚህም መሰረት በጉዳይ ላይ ከምዕመኑ ጋር ለመነጋገር ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው ኅዳር ፳፭፥ ፳፻፰ ዓ.ም ልዩ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርቶ ስለ ቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስትያን በትሮንዳሔም የቤተ ክርስትያን መዋቅርና የቤተ ክርስቲያኗን የበላይ ጠባቂ በግልጽ ስለ ማሳወቅ በሚል ርዕስ አባቶች በተገኙበት አወያይቷል። በዕለቱም ስለሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት እንዲሁም ስለቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስትያን በትሮንዳሔም የቤተ ክርስቲያን መዋቅር ጉዳይ ገለፃ ተሰጥቶ ግልፅ ውይይት ተደርጓል። ጠቅላላ ጉባኤውም የትሮንዳሔም ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፕትርክናው ኢትዮጵያ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስትያን ቅዱስ ሲኖዶስ ስር ቤተ ክርስቲያናዊ መዋቅርን ጠብቃና አክብራ መተዳደር አለባት በማለት ምልዓተ ጉባኤው ወስኗል።

 

 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መዋቅር ስር መሆናችንን ስለማሳወቅ ለብጹዕ አቡነ እንጦንስ ለሰ/ሰ/ምዕ/ አውሮፓ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ የተጻፈ ደብዳቤ።

በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ በትሮንዳሄም ተከታታይ መንፈሳዊ ጉባዔ ተካሄደ

በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሄም ለተከታታይ ሁለት ሳምንታት፤ ህዳር 18-19/2008ዓ.ም (November 28-29, 2015) እና ህዳር 25-26/ 2008ዓ.ም (December 05-06/2015) ልዩ መንፈሳዊ ጉባኤ በትሮንዳሄምና በአካባቢው የሚገኙ ምዕመናን በተገኙበት ተካሄደ። በጉባኤው መጀመርያ ቀን ቅዳሜ ህዳር 18 በአባታችን መልዓከ ሃይል መምህር አባ ዘድንግል (በጣልያን ባሪ ከተማበሚገኘው በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ) እና በዲ/ን ዶ/ር አለማየሁ በጸሎተ ኪዳን ተጀምሯል። በእለቱም በዲ/ን ዶ/ር አለማየሁ እና በአባታችን በአባ ዘድንግል ትምህርተ ወንጌል ሰፋ ባለ መልኩተሰጥቷል። እንዲሁም በአጥቢያው መዘምራን ያሬዳዊ መዝሙራት ከቀረቡ በኋላ የእለቱን መርሃ ግብር አባታችን በጸሎት አሳርገው ጉባኤው ተጠናቋል።

 ጉባኤው በመቀጠል እሁድ፣ ህዳር 19 በጠዋቱ የቅዳሴ ስርዓት ከተከናወነ በኋላ በአባታችን አባ ዘድንግል ሰፋ ያለ ትምህርት ተሰጥቶ የዕለቱ ጉባኤ ፍጻሜ ሆኗል።

 በቀጣዩ ሳምንት፤ ቅዳሜ ህዳር 25 ጠዋት ጸሎተ ኪዳን ደርሶ ከሰዓት በኋላ ደግሞ በቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደራዊ መዋቅር ላይ ያተኮረ ጠቅላላ ጉባኤ ተካሂዷል። የመንፈሳዊ ሰበካ ጉባኤው ስለ ቤተ ክርስቲያናችን ታሪክና በመዋቅር ስር መሆናችን ለቤተ ክርስቲያናችን ያለውን አስፈላጊነት እንዲሁም ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አንጻር እንዴት እንደሚታይ አጠር ያለ ማብራሪያ ለምዕመናን በመግለጽ ሰፊ ውይይት እንዲካሄድ ተደርጓል። በተነሱ ጥያቄዎችም ላይ በአባታችን መልዓከ ሃይል አባ ዘድንግል እና በወንድማችን ዲ/ን ሰሎሞን ገብረሚካኤል ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንንና ቃለ ዓዋዲን መሰረት አድርጎ ለጠቅላላ ጉባኤው በዝርዝር ግንዛቤ ተሰጥቷል። ከዚህም በመነሳት አንዲት፣ ቅድስትና ሐዋርያዊት የሆነች ቤተ ክርስቲያናችን በመዋቅር ታቅፋ ትተዳደር ዘንድ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ያን ቅዱስ ሲኖዶስ ስርእንድትሆን በማለት ጠቅላላ ጉባኤው ወስኗል።

  በጉባኤው መጨረሻም ቀን ዕሁድ ጠዋት ስርዓተ ቅዳሴ ተከናውኖ በአባ ዘድንግል የወንጌል ትምህርት እንዲሁም በዲ/ንሰሎሞን ያሬዳዊ መዝሙር ከቀረበ በኋላ መርሃ ግብሩ በጸሎት ተፈጽሟል።

የጉባዔውን አከባበር በፎቶ ይመልከቱ!

የ፳፻፰ ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል በደማቅ ሁኔታ ተከበረ

የቅዱስ ጊዮርጊስ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሔም የ ፳፻፰ ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል ከኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በመጡ ካህናት እና መዘምራን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሔም የሰንበት ት/ቤት መዘምራን፣ ከትሮንዳሔምና አካባቢው በተገኙ በርካታ ምእመናን እሁድ መስከረም ፲፮ በታላቅ ድምቀት ተከበረ።
በዓሉ እሁድ እለት ከሰዓት በኋላ በካህናት አባቶች ጸሎት የተጀመረ ሲሆን የቅዱስ ጊዮርጊስ አጥቢያ መዘምራን በዓሉን የተመለከቱ መዝሙራትን አቅርበዋል፣ የወንጌል ትምህርት ደግሞ ሥርዓተ ጸሎቱን በመሩት አባታችን ቀሲስ ተስፋዬ ከተሰጠ በኋላ በቅዱስ ሚካኤል የኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን መዘምራን እንዲሁ በዓሉን የሚያወድሱ ያሬዳዊ ዝማሬዎች ቀርበዋል።በማስከተልም ደመራው ተባርኮ የተለኮሰ ሲሆን መዘምራንና መላው ምእመንም በጋራ በመዘመር በዓሉን አድምቀውት አምሽተዋል፤በመጨረሻም ምእመናኑ ለበዓሉ የተዘጋጀውን ዝክር ቀምሰው ወደ የመጡበት በሰላም ተሸኝተዋል።
በዚሁ አጋጣሚ በተለያዩ መንገዶች ለዝግጅቱ መሳካት ብሎም ለበዓሉ ድምቀት ላደረጋችሁት መንፈሳዊ አስትዋጾ ሁሉ በሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ ስም ልባዊ ምስጋና ማቅረብ እንወዳለን።

የበዓሉን ዝግጅት በፎቶ ይመልከቱ!

የ፫ ቀናት መንፈሳዊ ጉባዔ ተካሄደ፤ የ፳፻፰ ዓ.ም ቅዱስ ዮሐንስ በዓልም በድምቀት ተከበረ

በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል።

የምድረ በዳ ተራሮች ይረካሉ፥ ኮረብቶችም በደስታ ይታጠቃሉ።

መዝ ፷፭፥፲፩

እንኳን ለአዲሱ ዓመት በሰላምና በጤና አደረሳችሁ።

የቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በትሮንዳሔም ከጷግሜ ፮፥፳፻፯ ዓ.ም እስከ መስከረም ፪፥፳፻፰ ዓ.ም ለሦስት ተከታታይ ቀናት የቆየ መንፈሳዊ ጉባኤና የአዲስ ዓመት ክብረ በዓል ከኢትዮጵያ ለመንፈሳዊ አገልግሎት ተጋብዘው ወደ አውሮፓ በመጡት መምህር (ቀሲስ) ለማ በሱፍቃድ አካሄደ። በአዲስ አመት ዋዜማ በስብከተ ወንጌል የተጀመረው ጉባዔ ቅዳሜ መስከረም ፩፥፳፻፰ ዓ.ም ሲቀጥል መርሐ ግብሩ በኪዳን ተጀምሮ፣ የአመቱ ባሕረ ሃሳብ ወጥቶ ስለቤተክርስቲያናችን ዘመን አቆጣጠር ትምህርት ተሰጥቷል። የእሁድ መርሐ ግብርም እንዲሁ በኪዳን ጸሎት ተጀምሮ ትምህርት ከተሰጠ በኋላ በተለይም በዓሉን የሚያስታውሱ መዝሙሮች ተዘምረው የጉባዔው ፍጻሜ ሆኗል።

መርሃግብሩን በፎቶ ይመልከቱ