የ፳፻፰ ዓ.ም ጰራቅሊጦስ በዓል በድምቀት ተከበረ

በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሔም የ፳፻፰ ዓ.ም ጰራቅሊጦስ በዓል ሰኔ ፲፩፥፳፻፰ ዓ.ም (June 18, 2016) በቅዳሴ፣ በያሬዳዊ ዝማሬዎችና በስብከት ተከበረ። በዕለቱ ከዴንማርክ የተጋብዙት አባ ዘሚካኤል ዴሬሳ ፣ ከቅዱስ ሚካኤል የኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ዲያቆናት እንዲሁም በትሮንዳሄምና አካባቢው የሚኖሩ ምእመናን የተገኙ ሲሆን መርሐ ግብሩ ከንጋቱ 12:30 (06:30AM) ሰዓት በጸሎትና በምንባባት ከተጀመረ በኋላ በቅዳሴ መርሃ ግብር እስከ ረፋድ ድረስ ቀጥሏል።

ከቅዳሴ ሥርዓቱ በኋላ ዕለቱን የተመለከቱ ያሬዳዊ ዝማሬዎች በጋራ ከተዘመሩ በኋላ በአባታችን አባ ዘሚካኤል ቀኑን የተመለከተ ሰፋ ያለ የወንጌል ትምህርትና ምክር ተሰጥቷል። በመጨረሻም የማሳረጊያ ጸሎት ተደርጎ የዕለቱ መርሃ ግብር ፍጻሜ ሆኗል። በዓሉን ለመካፈል የተገኘውም ህዝበ ክርስቲያን የተዘጋጀውን ጸበል ጸዲቅ እየቀመሰ ወደየቤቱ በሰላም ተመልሷል።

የበዓሉን አከባበር በፎቶ ይመልከቱ!