የጥምቀት በዓል በኖርዌይ በድምቀት ተከበረ
በኖርዌይ በተለያዩ ከተማ የሚገኙት ስድስት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያናት ማለትም የኦስሎ ቅዱስ ገብርኤል፤ የስታቫንጋር መድኃኔዓለም፤ የክርስቲያንሳንድ ቅድስት ድንግል ማርያም፤ የበርገን እመቤታችንና ቅዱስ ሚካኤል እና የትሮንዳሔም ቅዱስ ጊዮርጊስ ታቦታት አንድ ላይ በመሆን የጌታችን የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን በዓለ ጥምቀት በበርገንበታላቅ ድምቀት አከበሩ። በዓሉ በኖርዌይና ከተለያዩ ሃገራት በመጡ አባቶች ካህናትና ምእመናን በተገኙበት በቤተ ክርስቲያናችን ስርዓት መሰረት ከከተራ ጀምሮ ማለትም ጥር ፲ እና ፲፩ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም በደማቅ መንፈሳዊ አገልግሎት ተከበረ። የጥምቀት በዓል በኖርዌይ በአንድነት መከበር የጀመረው በ፳፻፬ ዓ.ም በኦስሎ ከተማ ሲሆን እንደዚህ ቁጥራቸው በዛ ባሉ ታቦታት ሲከበር ግን የመጀመሪያ ነው። ይህ በዓል ባለፈው ዓመትም በስታቫንገር እንደዚሁ በደማቅ ሁኔታ ተከብሮ እንደነበር ይታወሳል።