የ፳፻፱ የጌታችን ስቅለት እና ትንሣኤ በዓላት በቤተክርስቲያናችን በደማቁ ተከበረ

ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን

ሞተ ወኬዶ ለሞት

ለእለ ውስተ መቃብር

ወሃበ ሕይወተ ዘለዓለመ ዕረፍተ።

የ፳፻፱ ዓ.ም የጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት እና ትንሣኤ በዓላት በቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በትሮንዳሔም በድምቀት ተከበረ። በዓላቱ ከስዊድን ተጋብዘው በመጡት አባታችን መልአከ ህይወት ፍስሐ አባ ገብረማርያም ቢምረው እና በርካታ ቁጥር ባለው የትሮንዳሄምና አካባቢው ምእመን ሱታፌ በተለያዩ አገልግሎቶች ተከብሯል።

ዕለተ ዓርብ ሚያዝያ ፮፥፳፻፱ ዓ.ም በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መሠረት የጌታችንን ስቅለት በሚያወሱ ምንባባት፣ ሕማሙን በሚዘክሩ ጸሎቶች እንዲሁም በስግደት ያለፈ ሲሆን፤ በመጨረሻም ዕለቱን የተመለከተ ትምህርት ተሰጥቶ በቡራኬ የዕለቱ መርሃ ግብር ተፈጽሟል።

ቅዳሜ ምሽት ከ20:00 ሰዓት ጀምሮ የጌታችንን ትንሣኤ የሚያወድስ ሥርዓት ከምንባባትና ወረቦች ጋር ከተከናወነ በኋላ በሥርዓተ ቅዳሴና ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተፈጽሟል። በዓሉን ለመካፈል የተገኘውም ህዝበ ክርስቲያን ለበዓሉ የተዘጋጀውን ጸበል ጸዲቅ ቀምሰው ወደየቤታቸው በሰላም ተመልሰዋል።

የበዓሉን አከባበር በፎት ይመልከቱ!