ትንሣኤ

“እንደተናገረ ተነስቷል።” ማቴ  28 ፥ 6
ትንሣኤ ማለት ቀጥታ የቃሉ ትርጉም መነሣት ማለት ነው።

ብዙዎቻችንም እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው አደረሰን አደረሳችሁ እያልን እና እየተባባልን  ነው። ፖለቲከኛውም፣ ሰባኪውም፣ ጳጳሱም፣ ዘማሪውም  ዘፋኙም፣  አርቲስቱም፣ አክቲቪስቱም ሁሉም እንኳን አደረሳችሁ እያለ ነው። ጥሩ ነው ፥ ለምን ይባላል ማለት አይገባም ፥ ደስ ይላል ፥ መጠያየቁ  መተሳሰቡ ከልብ ከሆነ !! በሌላ መልኩ መድረስ የሚለው ቃል ናፋቂ ሆኗል ፥ ውሎ መግባት ፣ አድሮ  መገኘት ፣ ተኝቶ መነሳት ፣ ቁሞ መሔድ  ብርቅ የሆነበት ዘመን ላይ ደርሰናል።

➾  ጌታ ተነሣ ስንል እኛም መነሣት አለብን።  ከከፋፋይነት መቃብር ወጥተን  አንድ የሚያደርገን  ሐሳብ  መኖር  አለበት ።

  • በቂም በቀል እና በሴራ መቃብር ውስጥ ሆነን እንኳን አደረሳችሁ ብንባባል  የውሸት የይሁዳ ሰላምታ ይሆናል ።
  • እንደ ይሁዳ በልባችን ፥ ጥላቻ ፥ ፍቅረ  ነዋይ ፥ ቂምና በቀል ፥ ተንኮል ፥ ውሸት ፥ ሐሜት ፥ ሐሰት ፥ ትውዝፍት ፥ ሱሰኝነት ፥ ጣዖትን ፥ ማምለክ ፥  ምዋርት ፥ ጥል ፥ ክርክር፥ ቅንዓት፥ ቁጣ፥ አድመኛነት፥ መለያየት፥ መናፍቅነት፥ ምቀኝነት፥ መግደል፥ ስካር፥ ዘፋኝነት ፥  እያለ  በምንም አይነት መንገድ  የእውነት ሰላምታ ሊሆን አይችልም ስለዚህ  ከመቃብር እንውጣ ።  ያንጊዜ ትንሣኤያችን  በግልጥ  ቅዱሳት አንስት የሚያዩት ሐዋርያት የሚመልከቱት ይሆናል። በመቃብር ሆነን ስለ ትንሣኤ ብናወራ  እውነት አይሆንም  አያምርብንም።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተነሣ እኛም  በትንሣኤ ልቡና እንነሣ። የዘረኝነት፣ የውሸት፣ የጥላቻ፥ የበቀል፣ የሐሜት፣ የከንቱ ውዳሴ፣ የትዕቢት፣ የራስ ወዳድነት መቃብርን ፈንቅለን እንውጣ  ፣ በአፋችን እንኳን አደረሳችሁ እየተባባልን በልባችን ግን ቀጣይ ዓመት እንዳንደርስ እየተገዳደን ከሆነ ግን ይሁዳነት ነው። ይሁዳ ጌታን የሸጠው በአፉ ሰላም እያለ ነው ። ሁሉም ከተንኮል፣ ከሽንገላ መቃብር ይውጣ እና የፍቅር ትንሣኤን ይነሣ። እግዚአብሔር  የፍቅር  ትንሣኤ እንድናከብር አምላካችን ያድለን።

«እንደ ተናገረ ተነሥቶአልና በዚህ የለም፤ የተኛበትን ስፍራ ኑና እዩ። ፈጥናችሁም ሂዱና፡— ከሙታን ተነሣ፥ እነሆም፥ ወደ ገሊላ ይቀድማችኋል በዚያም ታዩታላችሁ፥ ብላችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው።»  የማቴዎስ ወንጌል 28:6-7

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም በጤና አደረሳችሁ!  አሜን ።

ይቆየን።