ምኵራብ

ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ፤
ቦአ ኢየሱስ ምኵራበ አይሁድ፤ወመሐረ ቃለ ሃይማኖት፤ወይቤሎሙ ምጽዋተ አበድር እመሥዋዕት፤አነ ውእቱ እግዚኣ ለሰንበት ወአቡሃ ለምሕረት፤እግዚኣ ውእቱ ለሰንበት ወልደ እጓለ እመሕያው፤ኢትግበሩ ቤተ አቡየ ቤተ ምሥያጥ ቤትየሰ ቤተ ጸሎት ይሰመይ፤ቦአ ምኲራቦሙ ወገሠጾሙ ያርምሙ፤አንከሩ ምሕሮቶ ሞገሰ ቃሉ ወጣዕመ ነገሩ ወሣዕሣዐ አፉሁ።

ትርጉም
ኢየሱስ ወደ አይሁድ ምኵራብ ገባ፤የሃማኖት ትምህርትን አስተማረ፤ከመሥዋዕት ይልቅ ምጽዋትን እወዳለሁ አላቸው፤የሰንበት ጌታ የይቅርታ አባት እኔ ነኝ፤የሰው ልጅ የሰንበት ጌታ ነው፤የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት፤ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች፤ወደምኵራባቸው ገባ፤ዝም ይሉ ዘንድም ገሠጻቸው፤ትምህርቱን የቃሉን ሞገስ የነገሩን ጣዕም የአንደበቱን ቅልጥፍና አደነቁ።
(ቅዱስ ያሬድ)

➾ ወይቤሎሙ ምጽዋተ አበድር እመሥዋዕት ፣
ከመሥዋዕት ይልቅ ምጽዋትን እወዳለሁ አላቸው

➣ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለፋሲካ በዓል ወደ ኢየሩሳሌም ወደምኵራብ ገባ ነገር ግን በምኵራብ ወርቅና ብር የሚለውጡትን በጉን በሬውን ርግቡን የሚሸጡትን አየ እሱም የአባቴን ቤት ወይም ቤቴ የጸሎት ቤት ነው የጸሎት ቤት ይባላል እናንተ ግን የገበያ አዳራሽ የሌቦች ዋሻ የቀማኞች መሸሻ አደረጋችሁት ብሎ
እየገረፈ አስወጣቸው እና ከመሥዋዕት ይልቅ ምጽዋትን እወዳለሁ አላቸው ይላል ለምን እንዲህ አለ ብንል ለመሥዋዕት የሚያቀርቡ ከዚህ እየገዙ ነበር ፣
➢ ለበዓል የሚወጡ ሰዎች ከሩቅ ቦታ የሁለት ቀን የሶስት ቀን የሳምንት ጎዳና እየነዱ መጥተው ሲደርሱ በዚያ ያሉ የጊዜው ነጋዴዎች ይኸማ ከስቷል ቀጥኗል ደክሟል ለመሥዋዕት አይሆንም ይሏቸዋል፣
➣ አና ምን ይሻላል ሲሏቸው እኛጋ የሰባ የወፈረ ያማረ ለመሥዋዕት የሚሆን አለን በሁለት አንድ ለውጣችሁ ወሰዱና ሠው እያሉ ምክንያት እየፈጠሩ ያጭበረብሩ ነበር ጌታ ይህን አይቶ ከመሥዋዕት ይልቅ ለሰዎች ማሰብን ለሰዎች መስጠትን ለሌሎች መራራትን ለሌለው ማካፈልን እወዳለሁ እንጅ እናንተ በማጭበርበር የምትነገዱበትን አይደለም ብሎ እየገረፈ አስወጣቸው ይላል ፣
➾ ስለዚህ ዛሬ ቤተ መቅደሱን ጌታችን ኢየሱስ ያጸዳበት ቀን ነው።
➢ አዎ ቤተ መቅደሱ በነጋዴዎች ተሞልቷል መቅደሱ በሌቦች በአጭበርባሪዎች በአስመሳዮች በግብዞች በውሸታሞች ተሞልቷል መጽዳት ይገባዋል።
መቅደሱ ለታለመለት አላማ ለምስጋና ለጸሎት የተገባ ሊሆን ያስፈልጋል ፣፣
➢ አንድም መቅደስ ሰውነታችን የተለያዩ ችግሮች ነግሠውበታል ውሸት ሐሜት ስርቆት ክፋት ተንኮል ምቀኝነት ዘረኝነት ሌብነት ዝሙት ሱሰኝነት በአጠቃላይ ምልዓተ ኃጢአት ሞልቶታል መጽዳት አለበት ።
➣ አሁን አሁን አብዛኛዎቻችን ሀሳባችን እግዚአብሔር በቤተክርስቲያን ውስጥ ያሉ አገልጋዮችን ስለእኛ ሕይወት መጥፋትም ሆነ ለሚሰራው ጥፋት ተጠያቂ በማድረግ እነርሱን እንደ አይሁድ በጅራፍም ሆነ በሥልጣኑ እንዲገሥፃቸው እንፈልጋለን ነገር ግን በሰውነታችን ፣በልቡናችን ላቆምነው ጣኦት፣ሕዋሳቶቻችን ጽድቅን በርኩሰት፣ጾምን በሆዳምነት፣ዕውቀትን በድንቁርና እየለዋወጥን ላለን ሰዎችምኮ ተግሣጽ አለብን ።
ሕዋሳቶቻችንን በምጽዋት ፣ በፆም ፣ በጸሎት፣ በስግደት ያነጻን እንደሆነ እግዚአብሔር ደግሞ ወደ ሕይወታችን የሚገባው በጅራፍ፣በተግሣጽ ሳይሆን በምሕረት በጸጋ ይሆናል እንዲሁም የሚፈታተኑንን ኀጣውእን ፣ ርኩሳትን አጋንንትን ከሰውነታችን ከቤቴ፣ከማደሪያዬ ምዕመን ውጣ በማለት ጠላታችን ኀጢአትን፣ዲያብሎስን ይገሥጽልናል። ሰውነታችን የልዩ ልዩ ክፉ ነገሮች መገበያያ ሆኗልና አምላካችን በመምህራን ትምህርት ፣በካህናት ሥልጣነ ክህነት ፤በምሕረቱ በቸርነቱ ያንጻን፣
እግዚአብሔር መቅደሱን ያጽዳልን ። አሜን

ይቆየን