“ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ፤ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም” (ማቴ. ፳፩፡፱)
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
የ2018 ዓ.ም የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቅድስት ከተማ ኢየሩሳሌም በታላቅ ክብርና ትሕትና መግባት የሚታሰብበት የሆሣዕና በዓል በኖርዌይ የትሮንደሃይም ምሥራቀ ፀሐይ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በታላቅ መንፈሳዊ ድምቀት ተከብሮ ውሏል።
“ሆሣዕና” የሚለው ቃል የዕብራይስጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙም “አቤቱ እባክህ አሁን አድን፤ አቤቱ እባክህ አሁን አቅና” ማለት ነው። በተጨማሪም “መድኃኒት” የሚለውን ትርጉም የሚይዝ ሲሆን፤ በዚህ ታላቅ ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የነቢያት ትንቢት ይፈጸም ዘንድ በትሕትና በአህያ ውርንጭላ ላይ ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም በክብር የገባበትን በማሰብ እለቱን በቅዳሴና በልዩ ልዩ መርሐ ግብራት ተከብሯል።
የዕለቱን በዓል ልዩ ካደረጉት መርሐ ግብራት መካከል የሰንበት ትምህርት ቤታችን ሕፃናትና ታዳጊ መዘምራን ያበረከቱት አገልግሎት ተጠቃሽ ነው። መዘምራኑ የድልና የሰላም ምልክት የሆነውን የዘንባባ ዝንጣፊ በእጃቸው ይዘውና የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ስዕለ አድኖ አጅበው በዝማሬ በዓሉን ሲያደምቁት ውለዋል። እነርሱን ተከትሎም የደብራችን አስተዳዳሪ ከዲያቆናት ጋር በመሆን የበዓለ ሆሣዕናን ሥርዓተ ዑደትን በደማቅ ሁኔታ መርተዋል።
ከዚህ አስደሳችና መንፈሳዊ የሆሣዕና በዓል በመቀጠል፣ የጌታችንን መከራና ሕማም የምናስብበት ቅድስት ሰሙነ ሕማማት መጀመሩ ታውጇል። በዚህም መሠረት ቤተ ክርስቲያናችን በሰሙነ ሕማማት ውስጥ በየዕለቱ ከጠዋቱ 8:00 AM ጀምሮ የሰሙነ ሕማማት የጸሎትና የስግደት መርሐ ግብር የምታከናውን መሆኑን ለምእመናን መልእክት ተላልፏል። ምእመናን በነዚህ ቀናት በመገኘት የበረከቱ ተካፋይ ትሆኑ ዘንድ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።
ልዑል እግዚአብሔር ጾማችንን፣ ጸሎታችንንና ስግደታችንን ተቀብሎ ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላምና በጤና እንዲያደርሰን የእርሱ መልካም ፈቃድ ይሁንልን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር አሜን።