ጸሎተ ሐሙስ

ጸሎተ ሐሙስ ክርስቶስ አምላካችን ራሱን ዝቅ አድርጎ የሐዋርያትን እግር ያጠበበት ዕለት ነው፡፡

በሕማማት ውስጥ ያለው ይህ ሐሙስ በተለያዩ ስያሜዎች ይጠራል፡፡

አንደኛ፦ጸሎተ ሐሙስ ይባላል፡፡ ምክንያቱም ጌታ ኀብስቱን በባረከ ጊዜ ስለጸለየ፤  እና  ከመያዙ አስቀድሞ በጌቴሴማኒ  ደቀ መዛሙርቱ ተኝተው እርሱ ግን  ተንበርክኮ  አባት ሆይ ብትወድስ ይች ጽዋ ከእኔ ትለፍ እያለ በሰው ልጆች  (በአዳም ልጆች) ተገብት ጸልዮልናል ፡፡
ሁለተኛው፦ትዕዛዝ ሐሙስ ይባላል ፡ ምክንያቱም ከኀጽበተ እግር በኋላ ጌታ እናንተም እንዲሁ አድርጉ ብሎ  አዝዟቸዋልና ነው ከዚያም ቀጥሎ በጌቴሴማኒም  ጌታ ወደ ፈተና እንዳትገቡ ጸልዩ ብሎ አዝዟቸዋል፤
ሦስተኛ፦ የምሥጢር ቀን ይባላል ፡ ሥርዓተ ቁርባንን ከሠራ በኋላ /ከመዝ ግብሩ ተዝካርየ/ ብሎ አዝዟል  እንዲሁም በዚህ ዕለት የተሰጡትን ሌሎችንም ትዕዛዛት ለማስታወስ ነው፡፡
አራተኛ፦ ኀጽበተ እግር  ሐሙስ ይባላል፡፡ ምክንያቱም በዚህ ቀን ጌታ የደቀመዛሙርቱን እግር ስላጠበ ባዘዘንም መሠረት ዛሬ በቤተክርስቲያን መታሰቢያውን እናደርጋለን ፡፡
አምስተኛ፦የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ ይባላል፡፡ በዚሁ ቀን ምሽት ጌታችን ‹‹ ሲበሉም ኢየሱስ እንጀራን አንሥቶ ባረከ ቈርሶም ለደቀ መዛሙርቱ ሰጠና፡— እንካችሁ፥ ብሉ ይህ ሥጋዬ ነው» አለ። ጽዋንም አንሥቶ አመስግኖም ሰጣቸው እንዲህም አለ፡— ‹‹ ሁላችሁ ከእርሱ ጠጡ፤ ስለ ብዙዎች ለኃጢአት ይቅርታ የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው።» (ማቴ.26:28) በማለት የሰጠንን ዘለዓለማዊ ኪዳን የሚያስታውስ ስያሜ ነው፡፡

ጌታችን ተጠምቆ ተጠመቁ ፣ ጾሞም ጹሙ እንዳለን ፣ ጸልዮ ጸልዩ፤ ሰግዶም ስገዱ ሲለን እንደዚሁም የደቀመዛሙርቱን እግር አጥቦ እናንተም እንዲህ አድርጉ ብሎ አርአያነቱን ሲያሳየን መምህረ ትሕትናነቱን ሲገልጥልን ነው፡፡ ዛሬም ከፓትርያርኩ ጀምሮ ሊቃነ ጳጳሳቱና ካህናቱ ሁሉም በየመዓርጋቸው የምእመናኑን እግር ዝቅ ብለው የሚያጥቡት የጌታን የትሕትና ሥራ ለማሰብ ነው፡፡

በዚህም መሠረት ይህንን ሥርዓቱን አብነት በማድረግ በዚች ቀን ዘጠኝ ሰዓት ሲሆን የሕፅበተ እግር ሥርዓቱ በሚከናወንበት ጊዜ ዲያቆኑ ውኃን ያቀርባል፤ በቀረበውም ውኃ ላይ ጸሎተ አኰቴት ይጸለያል፡፡ ወንጌል ተነብቦ ውኃው በካህኑ ወይም በሊቀ ጳጳሱ እጅ ይባረክና የሕጽበተ እግር ሥርዓቱ ከካህናት እስከ አናጕንስጢስ እንደዚሁም ከወንዶች እስከ ሴቶች ላሉት ምእመናን ሁሉ በካህናቱ እጅ ይከናወናል፡፡

ከበዓሉ በረከት  ያድለን አሜን፡፡