የ፳፻፲ ዓ.ም. የዘመን መለወጫና የመስቀል ደመራ በዓላት በደመቀ ሁኔታ ተከበሩ

በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የትሮንዳሔም ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የ፳፻፲ ዓ.ም አዲስ ዓመት በዓልን በማስመልከት እሁድ ጷጉሜን ፭፥፳፻፱ ዓ.ም ከዴንማርክ ተጋብዘው በመጡት አባ ዘሚካኤል የቅዳሴ አገልግሎትና የወንጌል ትምህርት የተሰጠ ሲሆን በዕለቱ ከትሮንዳሄምና አካባቢው የተገኙ ምዕመናንም በክብረ በዓሉ ላይ ታድመዋል። በተጨማሪም ቀኑን የተመለከቱ መዝሙሮችም በኅብረት ተዘምረዋል።

የመስቀል ደመራ በዓል ማክሰኞ መስከረም ፲፮፥፳፻፲ ዓ.ም በትሮንዳሔምና አካባቢው ከተገኙ ምዕመናን እንዲሁም ከቅዱስ ሚካኤል የኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በመጡ ምዕመናንና አገልጋዮች በደመቀ ሁኔታ ተከብሯል።

በዓሉ ማክሰኞ ዕለት ከሰዓት በኋላ 17:00 ሰዓት ላይ በጋራ ጸሎት የተጀመረ ሲሆን ከቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በመጡ አገልጋዮች ወረብና ቀኑን የሚያወሱ ንባቦች ቀርበዋል። በመቀጠልም የቅዱስ ጊዮርጊስ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን መዘምራን በዓሉን የተመለከተ መዝሙራትን ያቀረቡ ሲሆን ስለመስቀል በዓል የሚያስረዳ ስነ ጽሁፍም ቀርቧል። ቀጥሎም ደመራው በወረብና በመዝሙር ምስጋና በመታጀብ ተለኩሷል። መዘምራንና መላው ምእመንም በጋራ በመዘመር በዓሉን አድምቀውት አምሽተዋል። በመጨረሻም ምእመናኑ ለበዓሉ የተዘጋጀውን ዝክር ቀምሰው ወደ የመጡበት በሰላም ተሸኝተዋል።

በዚሁ አጋጣሚ በተለያዩ መንገዶች ለዝግጅቱ መሳካት ብሎም ለበዓሉ ድምቀት መንፈሳዊ አስትዋጽኦ ላበረከታችሁ ምዕመናን ሁሉ በሊቀ ሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ስም ልባዊ ምስጋናችንን ማቅረብ እንወዳለን።

የበዓላቱን አከባበር በፎቶ ይመልከቱ