እንኩዋን ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

”እነሆ ለህዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምስራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና…..”ሉቃ.2፤11

አስቀድሜ እንኩዋን ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ እላለሁ፡፡

የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ለሰው ልጆች ሁሉ መልካም ዜና ነው፡፡እርሱ የዓለምን ሁሉ ኃጢአት ለማስወገድ ተወለደ፡፡መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለቅድስት ድንግል ማርያም እንደ ነገራት ”….ስሙን ኢየሱስ ትዪዋለሽ እርሱም ታላቅ ይሆናል የልዑል ልጅም ይባላል..” የሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 2 ቀ. 32 ፡፡

ምናልባት ብዙ ጊዜ በተለምዶ ብቻ ገናን ወይም ልደትን ማክበር እየተስፋፋ የሄደ ጉዳይ ነው፡፡ ፈረንጆቹ በልደቱ ቀን ስጦታን መለዋወጥ ፤ ዛፎችን በደመቀ መብራት ማሸብረቅ፤ መብላት እና መጠጣት የመሳሰሉትን ጉዳዮች በመፈጸም ቀኑን ያሳልፋሉ፡፡ከበዛ ደግሞ ሳንታ ክሎስ ብለው ከሰየሙት የገና አባት ጋር ፎቶ መነሳት ሕጻናትን በውሸት ትርክት እንዲደነዝዙ በማድረግ የልደቱን ነገር የሚሸፍኑበትን የገና አባት የውሸት ትርክት እየነገሩ በማታለል….የልጆችን እውነቱን የማወቅ መብት በጊዜአዊ ብልጭልጭ ስጦታ ቀይረውታል፡፡
እንዲያውም አሁን አሁን ገና ማለት የልጆች ቀን ክፍለ ጊዜ እየመሰለ መጥቷል ፡፡ይህ ማለት ከዋናው ጉዳይ ጋር በእጅጉ የሰማይና የምድር ያህል እየተራራቅንና እየተለያየን ነው ማለት ነው፡፡

በአገራችንም ከዚህ ባልተናነሰ ሁኔታ ባህላዊ ምግቦችን በማዘጋጀት እና የገና ዛፎችን በማስጌጥ ሲዘፈን ሲጨፈር መዋል የተለመደ ነገር ሁኗል፡፡
ብቻ በሁሉም ጎን ማለት ይቻላል ፈር የለቀቀ ጉዳይ ይስተዋላል፡፡ ማለትም ከዋናው ጉዳይ ጋር ያለተገናኙ ነገሮች የበዓሉ ዋና ነገር ሆነው ቀርበዋልና፡፡

ከርስቶስን ከልደቱ ጀምሮ ሊገድለው ሲፈልግ የነበረ ሰይጣን፤ በኋላም ከሞት መነሳቱን በውሸት ዜና ተክቶ አልተነሳም ብለው እንዲናገሩ ሲጥር የነበረው ሰይጣን፤ አሁን ደግሞ ስልቱን ቀይሮ ሰዎች የልደቱን ትክክለኛ አላማ ቁም ነገር እንዳይረዱ በማድረግ በሚችለው ሁሉ እየሰራ ይገኛል፡፡በተወሰነ መልኩ የተሳካለትም ይመስላል፡፡

የልደቱን ምሥጢር ብዙዎች አልገባንም በቤተ ልሔም በግርግም የተወለደውን ሕፃን ከልባችንና ከቤት አስወጥተን ፤ በሰላሙ ፋንታ ሁከት በፍቅሩ ፋንታ ጥላቻውን በሕይወት ፋንታ ሞትን እያስፋፋን ወንድም ወንድሙን ልጅ አባቱን አባት ልጁን ወገን ወገኑን ለሞት አሳልፈን እየሰጠን።  ሰላም እምነት ደግነት የዋሀት ትሕትና ትዕግሥት እነዚህ ሁሉ ከልባችን ርቀው እነሱን ሳንመልስ ደግሞ ልደት ለማክበር ደፋ ቀና ማለት ምን ያህል ያለማስተዋል ይሆን ?
ምእመናን ሆይ ልብ ልንል የሚገባው ዋና ነገር የተወለደው ሕፃን ክርስቶስ በእኛ ልብ ስለመኖሩ እና የተወለደበት፣ የተሰቀለበት፣ የሞተበትና፣ የተነሳበት ትክክለኛ ዓላማ ገብቶናል ወይ የሚለው ቁም ነገር ነው፡፡
ተፈሥሒ ኦ ቤተ ልሔም ሀገሮሙ ለመላእክት እስመ በኀቤኪ ተወልደ ክርስቶስ ዳግማይ አዳም ከመ ያግብዖ ለአዳም ቀዳሚ ብእሲ እምድር ውስተ ገነት ፣
የመላእክት ሀገራቸው ቤተ ልሔም ሆይ ደስ ይበልሽ የቀደመ ሰው አዳምን ከምድር ወደገነት ከሞት ወደ ሕይወት ይመልሰው ዘንድ በአንች ከአንች ተወልዷልና ፤ ብሎ ቅዱስ ኤፍሬም እንዳመሰገነ እኛም ገብቶንና ተረድተነው ልናከብር ልናመሰግን ይገባል።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ከኃጢአት ለማዳን ተወለደ፤በእርሱ የኃጢአታችንን ስርየት እናገኛለን /የሐዋርያት ሥራ.10፤43/፤
መጽሐፍ በእርሱ የሚያምን ሁሉ አያፍርም ይላል፡፡ ሮሜ 10፤11

እርሱ የሕይወታችንም የክርስትናችንም መሠረት ነው፡፡ ያውም በልደቱ ቀን እርሱን ደስ የማያሰኘውን ጉዳይ እየፈጸምን እርሱን ከቤታችንና ከልባችን አስወጥተን ሰደን ወይም ቸል ብለን ድግሱ ላይ ብቻ የምናተኩር ከሆንን ምኑ ላይ ነው ክርስትናው? ያስብላል፤

ስለዚህ እግዚአብሔር ሆይ አንድያ ልጅህን ወደ ዓለም ልከህ ስለ ዓለም ሁሉ ኃጢአት ቤዛ እንዲሆን ፈቃድህ ስለ ሆነ እናመሰግንሃለን ፡ከልጅነት እስከ ዕውቀት የሰራነውን መተላለፍና ኃጢአት ይቅር በለን፡፡
ጌታ ሆይ ወደ ልባችን እንድትመልሰን እንማፀናለን ሁለጊዜ አንተን በማመን ጸንተን እንድንኖር እርዳን የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ፍቅር ከሁላችን ጋር ይሁን በዓሉን የበረከት የንስሐ የሥርየት በዓል ያድርግል ፡፡ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን። ይቆየን።

መልካም በዓል ያድርግልን