በዓለ ደብረ ዘይት

ደበረ ዘይት ትርጉሙ ፣ «ደብር » ማለት «ተራራ» ማለት ሲሆን «ዘይት» ማለት ደግሞ «የወይራ ዛፍ » ማለት ነው። ሲገናኝ «ደብረ ዘይት» ማለት የወይራ ዛፍ የሞላበት፣ የበዛበት፣ ወይም በወይራ ደን የተሸፈነ ተራራ ማለት ነው። « የወይራ ተራራ ማለት ይሆናል።

– ደብረ ዘይት ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ የሚገኝ ተራራ ሲሆን የጸሎተ ሐሙስ ማታ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጸለየበት ቦታና በኋላም የተያዘበት ቦተ ነው ፣
– ይህ ተራራ በመጽሐፍ ቅዱስ የሚገኙ ብዙ ሥራወቹ የተገለጡበት ቦታ ነው።
– ጌታችን ስለ ቤተ መቅደሱ መፍረስ፣ ስለ ዓለም ፍጻሜና ስለ ዳግም ምጽአት በዚህ ተራራ ላይ በግልጥ አስተምሯል (ማቴ.24፥3)።
– ከትንሣኤውም በኋላ በዓርባኛው ቀን በዚሁ ተራራ ላይ ወደ ሰማይ ዓርጓል (ሉቃ.24፥50)።
– ቀን በከታማና በገጠር ሲያስተምር ውሎ ሌሊት በዚሁ ተራራ ላይ ያድር ነበር ። በኋለኛው ዘመን በፍጻሜ ዘመን ነገረ ምጽአቱ ወይም በዚሁ ቦታ እንደሚገለጥ ትንቢት ተነግሯል።(ዘካ. 14፥3-5)።

– በዚህ ተራራ ላይ «እርሱም በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ፥ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው። ንገረን፥ ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድር ነው? አሉት» (ማቴ.24፥3)። ተብሎ ተእንደተጻፈ፣

– ለደቀ መዛሙርቱ የዳግም ምጽአቱን፣ የዓለምን ፈጻሜ፣ የትንሣኤ ሙታንን፣ ትምህርት በሰፊው በዚሁ ተራራ ላይ አስተምሯል ።

– ጌታ ይህንን ዓለም ለማሳለፍ ለሁሉም እንደ ሥራው ለመክፈል በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት ይመጣል፡፡
– ጊዜው ፦ ዘመነ ዮሐንስ፣ ወሩ ወርኃ መጋቢት፣ ዕለቱ ዕለተ እሑድ፣ ሰአቱ መንፈቀ ሌሊት፣ እንደሆነ ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡
– ምነው ‹‹ የሚያውቀው የለም ይል የለምን? ቢሉ! ማቴ 24 ÷ 42 እንዲህ ማለቱ ብዙ ፤ የዮሓንስ ዘመን ፤ ብዙ የመጋቢት ወር ፤ ብዙ ዕለተ እሑድ ፤ በዙ ሌሊቶች አሉና በዚህ ቀን ነው ብሎ ለይቶ የሚያውቅ የለም ለማለት ነው፡፡
– ንቃሕ መዋቲ ዘትነውም ባለ ጊዜ መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ደጉ ደግነቱን ክፉውም ክፋቱን ይዞ ይነሳል፡፡
– እያንዳንዱ የገዛ ራሱን ሸክም ሊሸከም ነውና። ገላትያ 6 ÷ 5

– ወንዱ የ30 ዓመት ሴቲቱ የ15 ዓመት ሆነው ጻድቃን ብርሃን ለብሰው ብርሃን ተጎናጽፈው ከፀሐይ 7 እጅ አብርተው ይነሳሉ ማቴ 13፡43 ኃጥአን ጨለማ ለብሰው ፍጹም ዲያብሎስን መስለው ይነሳሉ፡፡ ጻድቃን ስለሠሩት መልካም ሥራ ፦ ኑ የአባቴ ቡሩካን ብሎ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሳቸዋል፡፡ኃጥአንን ስለክፉ ሥራቸው ፦ ከኔ ሂዱ ብሎ ወደ ገሃነም ይልካቸዋል፡፡

– ጻድቃን ደስ ይላቸዋል ኃጥአን ግን ያዝናሉ ዋይ ዋይ እያሉ ደረት ይደቃሉ እንባቸውን ያፈሳሉ፡፡ የማይጠቅም ልቅሶ የማይረባ ኃዘን ነው ሰቅለው የገደሉትም አይሁድ ክብሩን አይተው ላይጠቀሙ ይጸጸታሉ፡፡
– እግዚአብሔር በዳግም ምጽአቱ ከሚያዝኑት ጋር ሳይሆን ከሚደሰቱት ፤ ከሚያለቅሱት ጋር ሳይሆን ከሚዘምሩት ከሚያመሰግኑት ጋር እድል ፈንታችንን ያድርግልን ከቅዱሳኑና ከሰማዕታቱ ጋር ለመቆም ያብቃን፡፡

አሜን ይቆየን ፣