ደብረ ዘይት

ደብረ ዘይት:- የዐቢይ ጾም አምስተኛ እሑድ የጌታችን ዳግም መምጣትና የዘመኑ ምልክት የሚነገርበት ቀን በመሆኑና   ጌታችን ስለ ዓለም መጨረሻና ስለ መምጣቱ ምልክት የተናገረው በደብረ ዘይት ተራራ ላይ በመሆኑ ዕለቱ ደብረ ዘይት እየተባለ ይጠራል። (ማቴ.24÷ 3)

ቅዱስ ያሬድ ዕለቱን ደብረ ዘይት ብሎ መሰየሙ ብቻ ሳይሆን በዕለቱም ያቀረበው ዝማሬ እንዲህ የሚል ነው፡-
“ወአመ ምጽአቱሰ ለወልደ እጓለ እመሕያው ይትከወስ ኲሉ ኃይለ ሰማያት ወምድር አሜሃ ይበክዩ ኲሎሙ ኃጥአነ ምድር ወይወርድ እግዚእነ እምሰማይ ዲበ ምድር በትእዛዙ ወበቃሉ ወበአእላፍ መላእክቲሁ በንፍሐተ ቀርን ዘእም ኀበ እግዚአብሔር ይምሐረነ አብ በይእቲ ሰዓት እሞተ ኃጢአት እስመ ገባሬሕይወት”

ትርጉም፡-
“የሰው ልጅ በሚመጣበት ጊዜ የሰማይና የምድር ሠራዊት ሁሉ ይነቃነቃል። ያን ጊዜ በምድር የሚኖሩ ኃጢአተኞች ሁሉ ያለቅሳሉ፡፡ጌታችንም ከአእላፍ መላእክት ጋር በትእዛዙና በቃሉ መሠረት ከሰማይ ወደ ምድር ይወርዳል። የእግዚአብሔር መለከትም ይሰማል፡፡ በዚያች ሰዓት እርሱ ያድነን። እርሱ የሕይወት ባለቤት ነውና።” በማለት ቅዱስ ያሬድ የዘመረው የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 24  ላይ ያለውን ነው።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚመጣው ከአሁን በፊት በመጣበት መንገድ  በትሕትና ሳይሆን በልዕልና በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ሳይሆን በምልዓት በስፋት በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት ነው። በከብቶች በረት ሊጣል ሳይሆን በደመና በዙፋን ተገልጦ ይመጣል። ስምዖን አረጋዊ እንደ ታቀፈው  ሳይሆን፣ ሰማይና ምድር የማይችሉት ሆኖ ። ከእናቱ ጡትን እየለመነ ሳይሆን፣ ለፍጥረት ሁሉ  ዋጋ ለመስጠት ። ከሄሮድስ ፊት የሚሸሽ ሆኖ  ሳይሆን፣ ሰማይና ምድር ሲያዩት ከፊቱ  የሚሸሹለት  ሆኖ  ይመጣል ። የጌታችን ዳግም ምጽአት ፡-

  1. የጸሎታችን መልስ ነው።
  2. የፍጥረት የምጥ ዕረፍት ነው።
  3. የዘመናት ናፍቆት መልስ ነው።
  4. የተስፋችን ፍጻሜ ነው።
  5. የእምነታችን ክብር ነው።
  6. የአዲስ ዓለም ጅማሬ ነው።
  7. የዘላለም ሕይወት መክፈቻ ነው፡፡

1.  የጸሎታችን መልስ ነው:-

ብዙ ሰዎች ክርስቶስ ዳግም ይመጣል ሲባሉ ይፈራሉ። ፍርሃታቸው ግን ለንስሐ አያዘጋጃቸውም። የጌታችን መምጣት ግን የጸሎታችን መልስ ነው። የምንፈራውና ይቅርብን የምንለው ሳይሆን በየዕለቱ “መንግሥትህ ትምጣ” እያልን የምንጸልይበት ትልቅ ርዕሳችን ነው። የዚህ ዓለም መንግሥት በግፍ ተጀምሮ በግፍ የሚጠናቀቅ፣ በውሸትና በሐሰተኛ ተስፋ ሰውን የሚያደክም፣ በጭካኔ ሲወዳደር የሚኖር፣ ደም በደም የሆነ መንገድ ነው። በዚህ ክፉ ሥርዓት የተጨነቁ ሁሉ ጽድቅና ሰላም የነገሠባትን የክርስቶስን መንግሥት ይናፍቃሉ (ሮሜ.14÷17) ። የክርስቶስ መንግሥቱ የምትገለጠው ጌታችን ምድራውያን ነገሥታትን አሳልፎ ንጉሠ ነገሥት ሆኖ በሚነግሥበት በዳግም ምጽአቱ ነው። ዳግም ምጽአቱ ምድራዊውን ሥርዓት አሳልፎ አንድ መንግሥትን በሁሉ የሚያፀና ነው።

2. የፍጥረት ምጥ ዕረፍት ነው:-

ሐዋርያው ጳውሎስ፡- “ የፍጥረት ናፍቆት የእግዚአብሔርን ልጆች መገለጥ ይጠባበቃልና” ይላል። (ሮሜ.8÷19)ዳግመኛም “ፍጥረት ሁሉ እስከ አሁን ድረስ አብሮ በመቃተትና በምጥ መኖሩን እናውቃለንና” ይላል ቁ.22) ። በሰው ኃጢአት የተጨነቀው ሰው ብቻ ሳይሆን ፍጥረት በሙሉ ነው። እንስሳቱ አራዊቱ ሁሉ የሰውን ኃጢአት ቅጣት እየተካፈሉ ነው። እነዚህ ሁሉ የሚያርፉት ክርስቶስ ልጆቹን በክብር በሚገልጥበት በምጽአቱ ቀን ነው። ስለዚህ ፍጥረት ሳይወድ በግድ የሰውን ማረፍ ይናፍቃል። የራሱም ዕረፍት ነውና። ዛሬ በብዙ ነገር እናለቅሳለን። ብዙ ጭንቀቶችም ከበውን እንኖራለን። የክርስቶስ መምጣት ግን የፍጥረት ምጥ ዕረፍት ነው።

3.  የዘመናት ናፍቆት እርካታ ነው:-

“ አሜን ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና” (ራእ.22÷20)። ዮሐንስ በራእዩ ስለሚመጣው የዘመናት ጣር ካየበኋላ የዚህ ሁሉ ማብቂያው ምንድነው? ብሎ ሲያስብ የጌታ መምጣት እንደሆነ ተረዳ። ስለዚህም ማራናታ አለ። የጌታችን መምጣት የመከራው ድንበር ነው። በመጀመሪያው  ምጽአቱ ሞት እንደ ተገደበ፣ በዳግመኛ ምጽአቱም መከራ ገደብ ያገኛል።

4.  የተስፋችን ፍጻሜ ነው:-

የምንጠባበቃቸው ብዙ ተስፋዎች ቢኖሩም ትልቁ ተስፋችን ክርስቶስ ነው፡። የምንጠብቃቸው ነገሮች ቢሆኑልን እንኳ ሌላ መመኘታችን አይቀርም። ክርስቶስ ከመጣልን ግን ምንም እንዳያምረን ለዘላለም ያረካናል። ሐዋርያው ቀዱስ ጳውሎስ፡- “የተባረከው ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ክብር መገለጥ እየጠበቅን ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል” (ቲቶ.2÷12 13) ይላል። ሰዎች ተስፋ ካላቸው ራሳቸውን ከሚጎዳ ነገር ይከላከላሉ። እንዲሁም ክርስቶስ ተስፋቸው የሆነ ይቀደሳሉ በኃጢአት መጫወት ተስፋ መቁረጥ ነው። የክርስቶስ ምጽአት የተስፋችን ፍጻሜ ነው። ለቤተ ክርስቲያን የቀረላት ተስፋ የክርስቶስ መምጣት ነው።

5.  የእምነታችን ክብር ነው:-

ጌታችን ዳግመኛ የሚመጣው በናቀን ዓለም ፊት እምነታችንን ሊያከብር ነው፡ የዘበቱብንና ያስጨነቁን ለዘላለም ያፍራሉ፡፡ዛሬ ቃሉን የረገጡ፣ ያን ቀን ፍርዱን መርገጥ አይችሉም። የእግዚአብሔር ልጆች የሆንም በዚያን ቀን በዘላለም ክብር ተውበን  እረኛችንን ተከትለን  ወደ ዘለዓለም  ደስታ  እንገባለን።

6.  የአዲስ ዓለም ጅማሬ ነው:-

በዮሐንስ ራእይ ላይ እንደ ተጻፈው “አዲስ ሰማይና አዲስ ምድርን አየሁ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና ባሕርም ወደፊት የለም” ይላል (ራእ.21÷1) ። አዲስ ነገር የሚያስፈልገው ፊተኛው ሲያረጅ ነው። ያረጀ ነገር መልኩ የወየበ፣ ጉልበቱ ያለቀ፣ ወደፊት ሊጠቅም የማይችል ነው። አሁን ፍጥረት አርጅቷል። በረዶ እየቀለጠ፣ የምድር ሙቀት እየጨለመ፣ መሬቱ ማዳበሪያ እየፈለገ፣ ሰውም በብዙ መድኃኒት እየኖረ ነው። ይህ የማርጀት ምልክት ነው። ይህን ሁሉ አዲስ የሚያደርገው የክርስቶስ መምጣት ነው። ሰውም ሞት ላይዘው በትንሣኤ፣ የሚመጣው ዓለምም ማርጀት ላያገኘው በአዲስነት ይኖራል።

7.  የዘላለም ሕይወት መክፈቻ ነው:-

ጌታችን ሲመጣ ዘላለማዊት የምትሆን መንግሥተ ሰማያት ትከፈታለች። ዛሬ በክርስቶስ ያመኑ በበጎ ሥራ የፀኑ አማንያን በጊዜያዊ ማረፊያቸው በገነት ይኖራሉ። ገነት ጊዜያዊ የነፍሳት ማረፊያ ናትና። ክርስቶስ ሲመጣ ገነትና ሲኦል ያልፋሉ። መንግሥተ ሰማያትና  ገሃነመ እሳት ይከፈታሉ (ማቴ. 25÷34.41) ።
ዘለዓለማዊው  ርስትም  ይከፈታል። ዘወትር አዲስ የሆነውን ጌታ እያየን በዘላለም ደስታ እንኖራለን።
የጌታችን መምጣት ብዙ ትርፎች ያሉት ወደማይነገርም ክብር የምንገባበት ነው። ዛሬ በዓለም ላይ የምናየው መከራና ሰቆቃ የምጽአቱ ዋዜማ ነው። ይህ ሁሉ ጭንቅ በክርስቶስ መምጣት ይጠናቀቃል።

የእግዚአብሔር ፍቅርና  ሰላም ከሁላችን ጋር ይሁን
አሜን ።

ኖላዊ

የዘመነ ስብከት ሦስተኛው ሰንበት ‹‹ኖላዊ›› ይባላል፡፡ ኖላዊ ማለት ‹‹እረኛ›› ወይም ‹‹ጠባቂ›› ማለት ሲሆን በዚህ ዕለት ቅዱሳን ነቢያት አምላክ ወልደ አምላክ እውነተኛ ጠባቂ ሆኖ ይገለጣል ብለው ትንቢት መናገራቸው እና ቅዱሳን ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት ኖላዊ ዘበአማን እውነተኛ ጠባቂ ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን ቤተክርስቲያናችን የምታስተምርበት ዕለት ነው፡፡

ነቢያት ራሳቸውንና ሕዝበ እስራኤልን ፤ ብሎም ዓለምን ፤ እንደ በጎች በመቁጠር ስለ እውነተኛው እረኛ መምጣት ትንቢት ተናግረዋል። በዚህ ሰንበት ከፍልሰተ ባቢሎን እስከ ልደተ ክርስቶስ ድረስ ያለው አሥራ አራት ትውልድ ይታሰባል። ቤተክርስቲያን ፦

“ ኖላዊሆሙ ለእስራኤል አፅምእ፤
ዘይርዕዮሙ ከመ አባግዕ ለዮሴፍ፤
ዘይነብር ላዕለ ኪሩቤል አስተርአየ።
በቅድመ ኤፍሬም ወብንያም ወምናሴ፤
አንሥእ ኀይለከ ፥ ወነዐ አድኅነነ።

እረኛ የሌለው የበግ መንጋ ተኵላ ነጣቂ እንዲበረታበት በበደሉ ምክንያት ከትጉህ እረኛው የተለየው የሰው ልጅም ሰብሳቢና የሚያሰማራ ጠባቂ እንዲኖረው ነቢያት ዮሴፍን እንደ መንጋ የምትመራ በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ የእስራኤል ጠባቂ ሆይ አድምጥ (መዝ 79፡1) በማለት ይማፀኑ እንደ ነበር ታስተምራለች።

ቸር ጠባቂ: የትንቢቱ ፍጻሜ ሲደርስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹መልካም እረኛ እኔ ነኝ፤ መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል›› ዮሐ፣ 10፥11 በማለት እውነተኛ አእረኛ እርሱ መሆኑን መልስ ሰጥቷል። ስለራሱም ‹‹መልካም እረኛ እኔ ነኝ፥ አብም እንደሚያውቀኝ እኔም አብን እንደማውቀው የራሴን በጎች አውቃለሁ የራሴም በጎች ያውቁኛል፤ ነፍሴንም ስለ በጎች አኖራለሁ።›› ዮሐ 10፡15 በማለት አስተምሯል፡፡

በልበ አምላክ ክቡር ዳዊትም “እግዚአብሔር እረኛዬ ነው የሚያሳጣኝ የለም በለመለመ መስክ ያሳድረኛል መዝ (22፡1) ተብሎ እንደተጻፈ በዚህ የጾም ወቅት አቤቱ ብርሀንህንና ጽድቅህን ላክ፣ ቸሩ እረኛችን ሆይ ተቅበዝብዘናልና እባክህ አስበን፣ እረኛ እንደሌላቸው በጎች ተበትነናልና ሰብስበን ጠፍተናልና ፈልገን አንተ እውነተኛ ሰላምህን ስጠን እያልን ሁሉን ወደ ሚችል ወደ እውነተኛው እረኛችን ወደ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በንስሐ ልንመለስ ይገባል።

ከተኩላዎች ተጠበቁ: ለክርስቲያኖች ሁሉ የታመነ ጠባቂ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ በተጨማሪም ‹‹በጎቼን ጠብቅ›› ብሎ በቅዱስ ጴጥሮስ በኩል አደራ የተሰጣቸው ካህናተ ቤተክርስቲያን የመንጋው ጠባቂ ናቸው፡፡ ነገር ግን በዚህ ሐሰተኛና ምንደኛ በበዛበት ዘመን እውነተኞቹን እረኞች ከተኩላዎቹ መለየት ያስፈልጋል፡፡ መልካም ዛፍ መልካም ፍሬ እንዲያፈራ መልካም እረኛም ለበጎቹ መልካምን ያደርጋል፡፡ ስለበጎቹም ይገደዋል ራሱን አሳልፎ ይሰጣል። (ማቴ 7፡15)፡ ተኩላ ግን በጎችን ሊጠብቅ ሳይሆን ሊነጥቅ እንደሚመጣ ሐሰተኞች እረኞችም ምዕመናንን ሊጠብቋቸው ሳይሆን ሊነጥቋቸው እየታገሉ ነው ፡፡ ነገር ግን መጨረሻቸው ጥፋት ስለሆነ ልናውቅባቸው ይገባል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ በገና ጾም ነቢያትም ሐዋርያትም ጾመው በረከት አግኝተውበታል፡፡ እኛ ምእመናንም እንደ እነርሱ በረከትን እናገኝ ዘንድ ይህንን ጾም መጾም እንደሚገባን የቤተክርስቲያን አባቶች ሥርዓት ሠርተውልናል፡፡ በዚህም መሠረት የነቢያት፣ የሐዋርያት፣ የጻድቃንና የሰማዕታት አምላክ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ሐዋርያት በረከት እንዲያሳትፈን፤ መንግሥቱንም እንዲያወርሰን ሁላችንም በዚህ በጾመ ነቢያት ወቅት በጾም በጸሎት ተወስነን እግዚአብሔርን ልንማጸነው ይገባል ከቅዱሳን ነቢያት በረከት ያድለን አሜን፣

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ብርሃን

የዘመነ ስብከት ሁለተኛው ሰንበት ‹‹ብርሃን›› ይባላል፡፡ ነቢያት የነፍሳችን ብርሃን ይወለዳል ብለው ስለመስበካቸው፣ እውነተኛ ብርሃን ይመጣል ብለው ሰለማስተማራቸው የሚታሰብበት ሲሆን በዚሁ ዕለት ኢየሱስ ክርስቶስ አማናዊ ብርሃን መሆኑ ይሰበካል፤ ይዘመራልም፡፡ ከዚሁ ጋር ዘመነ ብሉይ መከራ ሥጋ፣ መከራ ነፍስ የጸናበት የሰው ልጅ ብርሃን ከሆነው አምላክ ጋር የተራራቀበት ስለነበር ነቢያት የነበሩበትን ያን ዘመን ጨለማ ብለው በመግለጥ የነፍሳችን ብርሃን ይወለዳል፣ እውነተኛ ብርሃን ይመጣል ብለው ስለመስበካቸው የሚታሰብበት ቀን/ሳምንት/ ነው። በዚህ ሳምንት ከዳዊት እስከ ፍልሰተ ባቢሎን የነበረው ዘመን ( 14 ትውልድ) ይታሰብበታል፡፡

ነቢያት የአምላክን ማዳን ከአስተማሩባቸውና፣ ከገለጡባቸው መንገዶች አንዱ ብርሃን ነው፡፡ ልበ አምላክ ክቡር ዳዊትም ወደ ትክክለኛው መንገድ የሚመራ ብርሃን ወደ ዓለም እንዲመጣ “ብርሃንህንና ጽድቅህን ላክ” (መዝ 42፡3) በማለት ይጸልይ ነበር፡፡ ይህም ማለት ብርሃን፣ ጽድቅ፣ እውነት የሆነውን ልጅህን (ወልድን) ላክልን፤ እርሱ መርቶ ወደ መንግሥተ ሰማያት ያስገባን ዘንድ ማለት ነው (ኢሳ 49)፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም መጣ›› ብሎ እውነተኛ ብርሃን ስለሆነው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃንነት አስረግጦ ይነግረናል፣ (ዮሐ 1፡1-11)፡፡ ጌታችንም በመዋዕለ ስብከቱ ‹‹እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ፤ የሚከተለኝ የሕይወት ብርሃን ይሆንለታል እንጂ በጨለማ አይመላለስም›› (ዮሐ 8:12) ብሎ ስለ እርሱ እውነተኛ ብርሃንነትና አምላክነት በሚገባ አስተምሯል፡፡

በዚህ ዕለት ‹‹ከብርሃን የተገኘ ብርሃን›› እንዲሁም ‹‹የማይነገር ብርሃን›› የተባለ ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ ብርሃን መሆኑ አስረግጦልናል፡፡ ‹‹ብርሃን ወደ ዓለም መጣ›› ብሎ ቅዱስ ያሬድ እንዳስተማረን። ቅዱስ ኤፍሬምም በሰኞ ውዳሴ ማርያም ‹‹በዚህ አለም ለሚኖሩ ሰዎች ሁሉ የምታበራ እውነተኛ ብርሃን ስለሰው ፍቅር ወደ አለም የመጣህ፤ ፍጥረት ሁሉ በመምጣትህ ደስ አለው፡፡ አዳምን ከስሕተቱ አድነኽዋልና፡፡ ሔዋንንም ከሞት ጻዕረኝነት ነጻ አድርገኃታልና። የምንወለድበትን መንፈስ ሰጠኽን፤ ከመላዕክት ጋርም አመሰገንህ›› በማለት እኛም አባቶቻችንን አብነት አድርገን የሕይወታችን ብርሃን የሆነውን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እናመሰግናለን፡፡

እውነተኛ ብርሃን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ ረድኤቱን ይላክልን ፣ አሜን ፣

ዘመነ ስብከት

ከታህሳስ 7 እስከ ታህሳስ 26 ቀን ያለው ዘመን ዘመነ ስብከት ይባላል፡፡ ዘመነ ስብከት የተባለበት ምክንያትም ነቢያት የጌታን በሥጋ መምጣት አምልተውና አስፍተው በትንቢትና በትምህርት መስበካቸውን ቤተክርስቲያን እያሰበች ሰውን ለማዳን ወደ ምድር የመጣውን አምላክ የምትሰብክበት ወቅት በመሆኑ ነው፡፡

ስብከት: የዘመነ ስብከት የመጀመሪያው ሰንበት (እሑድ) ‹‹ስብከት›› ይባላል፡፡ በዚህ ቀንም በኦሪተ ሙሴ፣ በነቢያትም አስቀድሞ ስለ አካላዊ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆን ትንቢት ተነግሮ፣ ምሳሌ ተመስሎ፣ ሱባዔ ተቆጥሮ እንደ ነበር ይነገራል፤ ይሰበካልም፡፡

እምኦሪተ ሙሴ እስከ ነቢያት ሰበኩ ምጽአቶ ንህነ ነአምን ስብከቶ ፣ ከኦሪተ ሙሴ አንስቶ እስከ ነቢያት የወልደ እግዚአብሔርን መምጣት ሰበኩ አስተማሩ እኛም ሙሴና ነቢያት የሰበኩት ስብከት አምነን እንቀበላለን ፣እንዳለ (ቅዱስ ያሬድ )

ቅዱሳን ነቢያቱ አስቀድመው መምጣቱን ሰብከው ስለነበር ያንን ለማሰብ ይህ ዕለት ‹‹ስብከት›› ይባላል፣ ስብከት ማለት ሰውንና እግዚአብሔርን የሚያገናኝ ትምህርት ማለት ሲሆን በዚህ ሳምንት ከአብርሃም እስከ ዳዊት ባለው ትውልድ ውስጥ ስለ ክርስቶስ ሰው መሆን የተሰበከው ስብከት ይታሰባል፡፡

የነቢያት ስብከት: በዚህ ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሙሴ በሕግ ነቢያትም በትንቢት እንደ ጻፉለት የሚናገረው ወንጌል ይነበባል (ዮሐ 1፡44)፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊትም ‹‹ፈኑ እዴከ እም አርያም » እጅህን ከአርያም ላክ አድነኝም› (መዝ 143፡7) በማለት ስለክርስቶስ ማዳን በትንቢት መነጽር ተመልክቶ የዘመረው የመዝሙር ክፍል እንዲሁ ይሰበካል፡፡ ከዐበይት ነቢያት አንዱ የሆነው ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስም ‹‹ሰማዮችን ቀደህ ምነው ብትወርድ! ተራሮችም ምነው ቢናወጡ›› (ኢሳ 64፡1) ብሎ ስለክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት መውረድ፣ ከድንግል ማርያምም መወለድ የተናገረውን ትንቢት ቤተክርስቲያን ትሰብካለች፡፡

የቤተክርስቲያናችን ስብከት: ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ “እኛስ የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን” (2ኛ ቆሮ 4፡5) እንዳለው ቤተክርስቲያን በተለይ በዘመነ ስብከት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች የሰጠውንና የፈጸመውን የማዳን ተስፋ ትሰብካለች፡፡ ቅዱስ ያሬድም በመዝሙሩ “ከዓለም በፊት የነበረውንና መድኃኒት የሆነውን ወልድን እንሰብካለን” እንዳለ ቤተክርስቲያናችን ፣ በጊዜውም አለጊዜውም፣ በችግርም በደስታም ስለ ኃጢአታችን የሞተውንና አምላክ ወልደ አምላክ ክርስቶስን ትሰብካለች፤

አምላካችን እግዚአብሔር ከአባቶቻችን በረከየተ ያድለን፣ አሜን።

አሁንስ፥ ይላል እግዚአብሔር፥ በፍጹም ልባችሁ፥ በጾምም፥ በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ

በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

የተወደዳችሁ በዓለም ዙሪያ ያላችሁ ምእመናን ወምእመናት እንኳን ለጾመ ነቢያት በሰላም አደረሳችሁ አደረሰን !!

“ጾምሰ ተከልዖተ ብእሲ እመብልዕ በጊዜ ዕውቅ በውስተ ሕግ እንዘ ይትኤዘዝ ለዘሐገጎ ለሥርየተ አበሳ ወብዝኀ ዕሤት ፈቃዶ ኪያሁ ከመ ያድክም ኃይለ ፍትወት ወትትአዘዝ ለነፍስ ነባቢት።” ይኽም ማለት ጾምስ በሕግ ውስጥ በታወቀው ጊዜ የሰው ከምግብ መከልከል ነው። በደሉን ለማስተስረይ ዋጋውን ለማብዛት እርሱን ወድዶ ሕግን ለሠራለት እየታዘዘ የፈቲውን ኃይል ያደክም ዘንድ ለነባቢት ነፍስም ትታዘዝ ዘንድ። (ፍት. ነገ.ፍ.መ. አንቀጽ ፲ ወ ፭ቱ ቁጥ ፭፻፺፬)

የቤተ ክርስቲያናችን የሕግ መጽሐፍ እንደሚያስረዳን ጊዜ ወስኖ ወቅት ለይቶ አዋጅ አውጆ ቀኖና ሠርቶ ንስሐ ገበቶ መጾም እንደሚገባ በዚህም በረከት እንዳለው እንረዳለን። ነቢዩ ኢዩኤልም እንዲህ ይለናል፦

” አሁንስ፥ ይላል እግዚአብሔር፥ በፍጹም ልባችሁ፥ በጾምም፥ በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ። ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ፤ አምላካችሁም እግዚአብሔር ቸርና መሐሪ፥ ቁጣው የዘገየ፥ ምሕረቱም የበዛ፥ ለክፋትም የተጸጸተ ነውና ወደ እርሱ ተመለሱ። የሚመለስና የሚጸጸት እንደ ሆነ፥ ለአምላካችሁም ለእግዚአብሔር የእህልና የመጠጥ ቁርባን የሚሆነውን በረከት የሚያተርፍ እንደ ሆነ ማን ያውቃል? በጽዮን መለከትን ንፉ፥ ጾምንም ቀድሱ፥ ጉባኤውንም አውጁ፥ ሕዝቡንም አከማቹ፥ ማኅበሩንም ቀድሱ፥ ሽማግሌዎቹንም ሰብስቡ፥ ሕፃናቱንና ጡት የሚጠቡትን አከማቹ፤ ሙሽራው ከእልፍኙ፥ ሙሽራይቱም ከጫጉላዋ ይውጡ፣” ኢዩ ፪ ፥ ፲፪ – ፲፮

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህንኑ የነቢያትንና የሐዋርያትን ቃል መሠረት በማድረግ በአዋጅ ከደነገገቻቸው አጽዋማት አንዱ ጾመ ነቢያት (ጾመ ስብከት) (ጾመ ልደት) ተብሎ የሚጠራው ጾም ነው። የዚህ ጾም መሠረት ነቢያት አስቀድመው ስለ ጌታ ወደዚህ ዓለም መምጣት፣ ትንቢት ተናግረው፣ ሱባኤ ቆጥረው ፣ አንስእ ኀይለከ፣ ፈኑ እዴከ፣ስልጣንህን ግለጥ ልጅንህንም ላክልን እያሉ ነገረ ልደቱን (ርደቱን) በመጠባበቅ የጾሙት ጾም ነው ቤተ ክርስቲያንም ቅዱሳን ነቢያትን አብነት በማድረግ ትጾማለች ።

በዚህም መሠረት ቅዱሳን ነቢያት ኢሳይያስ፣ ኤርምያስ፣ ሚልክያስና ሌሎችም የጌታችን የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ልደት አስቀድመው በትንቢት ሲገልጹ በጾም፣ በጸሎትና በሱባኤ ነበር። በአጽዋማትና በበዓላት ቀኖናችን መሠረት እነርሱ ተስፋ አድርገው ድኅነቱን ለማየት፣ ቃሉን ለመስማት በትንቢት ተስፋ ያደረጉትን እኛ እንድናየው እንድንሰማው ስለፈቀደልን። ተስፋህን ለመፈጸም፣ ማዳንህን ለማየት፣ ቃልህን ለመስማት ያበቃኸን አምላካችን የልደትህ በረከት ተካፋዮች አድርገን፤ ደስም እናሰኝህ ዘንድ መላእክት በምድር ሰላም ለሰውም እርቅ ሆነ (ሉቃ ፪ ÷ ፲፬) ብለው እንዳመሰገኑህ እኛንም የሰላም ሰዎች አድርገን በኃጢአት የረከሰ ፣ሰውነታችንን፣ በክፋት የደነደነ ልቡናችንን በተንኮል የታጠረ ሕይወታችንን ከኃጢአት ከበደል አንጻን፣ በመሐሪነትህ፣ ማረን፣ ይቅር በለን፣ የቀደመ በደላችንን አታስብብን፣ ይቅርታህ ፈጥኖ ይደረግልን፣ በማለት እንጾማለን።

አባቶቻችን በደነገጉት የበዓላትና የአጽዋማት ቀኖና መሠረት የነቢያት ጾም አርባ ቀን እንዲሆን ደንግገዋል። ፵ው ቀን ጾመ ነቢያት፤ ፫ቱ ቀናት ጾመ አብርሃም ሶርያዊ፤ ፩ ቀን ጾመ ገሐድ በመባል ለ፵፬ ቀናት ይጾማል፣ (እንጾማለን)። የገና ጾመ ገሐድ ከጾሙ ተያይዞ የተቀመጠ እንጂ ለብቻው የተቀመጠ ባለመሆኑ አንዳንድ ሰዎች የገና ገሐድ የለውም ሲሉ ይሰማል ነገር ግን በፍትሕ መንፈሳዊ እንደተገለጠው እስከ የዓርብ ፀሐይ፣ (እስከ ይሠርቅ ኮከብ) በማለቱ ይታወቃል። ፍ.መን. አንድምታ አንቀጽ ፲፭ ÷ ፭፻ ፷፰

ስለዚህ « እስመ ተሐነጽክሙ ዲበ መሠረተ ሐዋርያት ወነቢያት እንዘ ክርስቶስ ርእሰ ማእዘንተ ሕንጻ። ዘቦቱ የኀድር ኵሉ ሕንጻ ወይጸንዕ ጽርሐ መቅደሱ ለእግዚአብሔር ፥ ወአንትሙሂ ቦቱ ተሐነጽክሙ ማኅደረ እግዚአብሔር በመንፈስ ቅዱስ።
፦ በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፥ የማዕዘኑም ራስ ድንጋይ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፤  በእርሱም ሕንጻ ሁሉ እየተጋጠመ በጌታ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንዲሆን ያድጋል፤ በእርሱም እናንተ ደግሞ ለእግዚአብሔር መኖሪያ ለመሆን በመንፈስ አብራችሁ ትሠራላችሁ።  (ኤፌሶን ፪ ፥ ፳  ) ብሎ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን ሁላችንም አባቶቻችን ነቢያትን እና ሐዋርያትን አብነት አድርገን በመጾም በመጸለይና በመስገድ በመመጽወት ለሌሎች በመራራት ራስን በመግዛት ልብንና ሕሊናን በማንጻት ያለኝ ይበቃኛል በማለት ቂም በቀልን በማራቅ፣ ከክፋትና ተንኮል፣ ምቀኝነት በመራቅ በንጹሕ ልብ ጾመን በረከት እንድናገኝ አምላካችን ይርዳን የአባቶቻችን በረከት አይለየን ለሀገር፣ ለወገን ፣ሰላሙን ይላክልን ፣

ሰላመ እግዚአብሔር አይለየን አሜን
ይቆየን
አባ ቀለመወርቅ

እንኳን ለታላቁ መልአክ ለቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል አደረሳችሁ አደረሰን !!

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ።

«ጥብዒኬ እም ወኢትናፍቂ  ንፈጽም ገድለነ ወስምዓነ»
‟እናቴ ሆይ! ገድላችን እንፈጽም ዘንድ ጨክኝ በርቺ አትጠራጠሪ  አናንያን፣ አዛርያንና ሚሳኤልን ያዳነ አምላክ ያድነናል”
(ቅዱስ ያሬድ)

እንኳን ለታላቁ መልአክ ለቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል አደረሳችሁ አደረሰን !!

በዛሬው ዕለት የቅዱስ ገብርኤልና የቅዱስ ቂርቆስ የቅድስት ኢየሉጣ አመታዊ ክብረ በዓል ነው።
በዚህ ቀን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ቅድስት እየሉጣንና ልጇን ቅዱስ ቂርቆስን ከሥጋ መከራ እንደታደጋቸው ከፈላ የብረት ጋን እንዳወጣቸው  ታሪክ ይናገራል።

ትምህርታዊ ጽሑፎች

ትምህርተ ሃይማኖት

ልዩ ልዩ